ዜና

"የኮሙኒኬሽን ስራችን ከሁነት ዘገባ ባሻገር የዞኑን ፀጋዎችን የማስተዋወቅ፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት መረጃን ለህዝብ ተደራሽ ማድረግ እና ህዝብና መንግስትን በመረጃ ማገናኘት ላይ ትኩረት ሊያደርግ ይገባል"          
አቶ ካሳሁን ቱጂ         

#ቡታጅራ ነሀሴ 14/2018          
የምስራቅ ጉራጌ ዞን መንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ የ2018 አፈፃፀም የገመገመ፣ ዕውቅናና ሽልማትን ያበረከተ ብሎም የ2019 በጀት ዓመት ጠቋሚ ዕቅድ ላይ የመከረ የአመራርና የፈፃሚ ማዘጋጃ መድረክ በዛሬው ዕለት አካሄዷል።         

የምስራቅ ጉራጌ ዞን መንግስት ኮሚኒኬሽን መምሪያ ኃላፊ አቶ ካሳሁን ቱጂ በውይይት መድረኩ ላይ እንደተናገሩት መድረኩ የነበረንን አፈፃፀም በመገምገም ለ2019 እቅዳችን በላቀ መልኩ ለመፈፀም የሚያግዙ ግብዓቶችን ያገኘንበት መድረክ ነው ያሉ ሲሆን የነበረን አፈፃፀም እንደተጠበቀ ሆኖ በቀጣይ ግን በዋናነት የኮሙኒኬሽን ስራችን ከሁነት ዘገባ ባሻገር የዞኑን ፀጋዎችን የማስተዋወቅ፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት መረጃን ለህዝብ ተደራሽ ማድረግ እና ህዝብና መንግስትን በመረጃ ማገናኘት ላይ ትኩረት ሊያደርግ ይገባል በማለት አስገንዝበዋል።         

ኃላፊው አቶ ካሳሁን አክለውም በዞናችን በ2018 በጀት ምርጫ 2018 እና የብሔር ብሔረሰቦች ቀንን የመሳሰሉ ትላልቅ ሁነቶችን በኮሙኒኬሽንና ሚዲያ ስራ ሽፋን በመስጠት ከፍተኛ አገልግሎት የሰጠንበት ነበር ያሉ ሲሆን በቀጣይም ለላቀ ስኬት መትጋት እንደሚገባ በመግለፀ በዞናችን በሁሉም አካባቢ የሚስተዋሉ ሀሰተኛ መረጃዎች መመከት የምንችለው ስለዞናችን ብሎም ስለወረዳና ከተሞቻችን ትክክለኛ ነባራዊ ሁኔታ፣ ስላሉን የተፈጥሮና ሠው ሠራሽ ፀጋዎች፤ ባህልና እሲቶች እንደሁም መንግስት እየሠራቸው ስላሉ የልማት ሥራዎች በሚዲያዎቻችን በማሰራጨት ለህዝብ ፈጣን መረጃን ተደራሽ በማድረግ እንደሆነ ገልፀዋል።         

የህዝብ አስተያየትንም በአግባቡ በመሰብሰብ ለሚመለከታቸው መ/ቤቶች በማደረስ ምላሽ እንዲያገኙ በትኩረት መስራትና የኮሚኒኬሽን ተቋም የእውነተኛ የመረጃ ምጭ ሆኖ እንዲያገለግል የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባልም ብለዋል።          

የዞኑ መንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ ም/ ኃላፊና የኮሚኒኬሽንና ሚዲያ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ኢብራሂም በድሩ በበኩላቸው የመንግስት ኮሚኒኬሽን ተቋም ዋነኛ ተግባር በህዝብና መንግስት መካከል እውነተኛ የመረጃ ፍሰት እንዲኖር ማድረግ እንደሆነ አስገንዝበዋል።         

ካሉብን በርካታ ምቹ ያልሆኑ ሁኔታዎች ሳንገደብ ባሉን ግብዓቶችና የሠው ኃይል በሚገባ በመጠቀም የሚጠበቅብንን የኮሚኒኬሽንና የሚዲያ ሥራዎቻችንን በመከወን ለህብረተሰባችን እርካታ መትጋት አለብን ብለዋል።         

በህዝብና በመንግስት መካከል ያሉት ግንኙነቶችን ለማጠናከር ከህዝብ የሚነሱ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በሚገባ ተደራጅተው በሚመለከታቸው ተቋማት ምላሽ እንዲያገኙ በማድረግ ረገድ የሚዲያ ሞኒተሪግና የህዝብ አስተያየት ተግባራት ትልቅ ድርሻ እንዳለው ታውቆ ሚናቸውን እንዲያሳድጉም አመላክተዋል።         

ከመድረኩ ተሳታፊ አካላትም በበጀት ዓመቱ ከዋናው ተግባራት በተጨማሪ በበርካታ ሁነቶችና የመንግስት ተልዕኮዎች የበዙበት ቢሆንም የመንግስት ኮሚኒኬሽን ተቋማት ኃላፊነታቸውን በሚገባ የተወጡበት በተለይም የዞኑ ኮሚኒኬሽን መምሪያው ትልቅ ድርሻ እንደነበረው ተገልጿል።         

በኮሚኒኬሽን መምሪያው የተደረጉ የክትትልና ድጋፍ ስራዎች በዞኑ መዋቅሮች ያሉ የኮሚኒኬሽን ተቋማት ክፍተቶቻቸውን በመለየት እንዲያስተካክሉ የተደረጉ ጥረቶች ጥሩ መሆኑን በመግለፅ በቀጣይም የክትትልና ድጋፉ ተግባር አጠናክሮ በማስቀጠል የሚያጋጥሙ ችግሮችን በጋራ እንዲፈቱ በማገዝ፤ ስልጠና ለሚያስፈልጋቸው የስልጠና ዕድል በማመቻቸት ለጥቅል ዞናዊ ስኬት መስራት እንደሚያስፈልግ ከመድረኩ ተሳታፊዎች አስተያየት ተሰጥቷል።         

በመድረኩ ለተነሱ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ምላሽና ማብራሪያ እንዲሁም በቀጣይ መሰራት ስላለባቸው ሥራዎች አቅጣጫ የተቀመጠ ሲሆን፤ የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ላይ መምሪያው ከወረዳና ከተማ አስተዳደር የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ጋር የግብ ስምምነት ተፈራርመዋል።         

በመጨረሻም በ2018 በጀት ዓመት መምሪያው ለነበረው ከፍተኛ አፈፃፀም ከፍተኛ ድጋፍ ላበረከቱ የዞን ተቋማትና ለወረዳና ከተማ አስተዳደር የኮሙኒኬሽን መዋቅሮች ሰርተፍኬት የተበረከተ ሲሆን እንዲሁም በዞኑ ካሉ መዋቅሮች ከፍተኛ አፈፃፀም በማስመዝገብ ከ1ኛ እስከ 3ኛ ደረጃ ለወጡ የዋንጫ ሽልማትና የዕውቅና ሰርተፍኬት በመስጠት መድረኩ ተጠናቋል።         

ዘገባው የምስራቅ ጉራጌ ዞን መንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ ነው።